Harari Attorney General

Government of Harari People Regional State

Latest News & Updates

Get Latest News & Updates​ from our page

የመምረጥ እና የመመረጥ መብት

Published on: February 11, 2026 at 4:57 PM
መግቢያ
ምርጫ ዜጎች በመረጧቸው ተወካዮች አማካኝነት ራሳቸውን በራሳቸው የማስተዳደር መብታቸውን በተግባር የሚያውሉበት መንገድ ነው። ዜጎች በመራጭነትም ሆነ በተመራጭነት የመሳተፍ መብታቸው ኢትዮጵያ ተቀብላ ባጸደቀቻቸው በአለም አቀፍ ሰብዓዊ መብቶች መግለጫ እና አለም አቀፍ የሰብዓዊና ፖለቲካ መብቶች ቃል ኪዳን እንዲሁም በአገራችን ሕገ-መንግሥት የተረጋገጠ መብት ነው።
የመምረጥና የመመረጥ መብት
በኢ.ፌ.ዴ.ሪ ህገ-መንግሥት አንቀጽ 38(1) መሠረት ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ዜጋ በቀለም፣ በዘር፣ በብሔር፣ በብሔረሰብ፣ በፆታ፣ በቋንቋ፣ በሀይማኖት፣ በፖለቲካ ወይም በሌላ አመለካከት ወይም በሌላ አቋም ላይ የተመሰረተ ልዩነት ሳይደረግበት
• በቀጥታ እና በነጻነት በመረጣቸው ተወካዮች አማካኝነት በህዝብ ጉዳይ አስተዳደር የመሳተፍ
• እድሜው 18 አመት ሲሞላው በሕግ መሰረት የመምረጥ
• በማናቸውም የመንግስት ደረጃ በየጊዜው በሚካሄድ ምርጫ የመምረጥና የመመረጥ መብት አለው።
ምርጫው ሁሉ አቀፍ፣ በሁሉም እኩልነት ላይ የተመሰረተ እና በሚስጥር ድምጽ አሰጣጥ መራጩ ፍቃዱን በነጻነት የሚገልጽበት ዋስትና የሚሰጥ መሆን እንዳለበት ተመልክቷል። ከዚህ አንፃር በምርጫ፣ የፖለቲካ ታርቲዎች ምዝገባ እና የምርጫ ሥነ ምግባር አዋጅ ቁጥር 1162/2011 በአዋጅ ቁጥር 1394/2017 እንደተሻሻለው በዝርዝር የተመለከቱ መስፈርቶችን ያሉ ሲሆን እንደሚከተለው እንመለከታቸዋለን፡፡
 የመምረጥ መብት
በአገራችን ሕገ-መንግሥት የመምረጥ መብት የኢትዮጵያዊ ዜግነት ላለው ብቻ የተሰጠ መብት በመሆኑ በዜግነት ኢትዮጵያዊ ያልሆነ ሰው በመራጭነት የመሳተፍ መብት የለውም። ከዚህ በተጨማሪ በመራጭነት ለመሳተፍ አስቀድሞ መሟላት ያለባቸው ቅድመ ሁኔታዎች ያሉ ሲሆን አነዚህ ቅድመ ሁኔታዎችም በአዋጅ ቁጥር 1162/2011 አንቀጽ 18 በአዋጅ ቁጥር 1394/2017 እንደተሻሻለው ላይ ተመልክተዋል።
በዚህ መሰረትም ማንኛውም፡-
• ኢትዮጵያዊ ዜጋ ከሆነ
• በድምጽ መስጫው ዕለት ዕድሜው 18 (አስራ ስምንት) አመትና ከዚያ በላይ ከሆነ
• በአንድ የምርጫ ክልል ቢያንስ ለስድስት ወር የኖረ ከሆነ
በመራጭነት የመሳተፍ መብት አለው፡፡ ሆኖም በአዕምሮ ህመም ምክንያት የመወሰን አቅም የሌለው መሆኑ ስልጣን ባለው አካል ወይም በበቂ ማስረጃ የተረጋገጠበት ሰውና የመምረጥ መብቱ በሕግ ወይም አግባብ ባለው ሕግ መሠረት በፍርድ ቤት ውሳኔ የተገደበበት ሰው በመራጭነት ተመዝግቦ በምርጫ የመሳተፍ መብት የሌለው መሆኑን ከአዋጁ አንቀጽ 18(3) መረዳት ይቻላል፡፡ እዚህ ላይ ልብ ሊባል የሚገባው የመምረጥ መብቱ የተረጋገጠለት ማንኛውም ሰው እስቀድሞ የመራጭነት ካርድ በእጁ ማድረግ የሚጠበቅበት ሲሆን በምርጫ ቀንም በምርጫ ጣቢያ ቀርቦ የፈለገውን ተመራጭ የመምረጥ መብት እንዳለው በሕገ-መንግሥቱም ሆነ በአዋጁ ላይ ተምልክቶ ይገኛል።
 የመመረጥ መብት
በኢ.ፌ.ዴ.ሪ ሕገ-መንግስት መሰረት የመመረጥ መብት የኢትዮጵያዊ ዜግነት ላለው ብቻ የተሰጠ መብት በመሆኑ በዜግነት ኢትዮጵያዊ ያልሆነ ሰው በተመራጭነት የመሳተፍ መብት የለውም። በኢትዮጵያ የምርጫ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባና የምርጫ ሥነ-ምግባር አዋጅ አንቀጽ 31 በአዋጅ ቁጥር 1394/2017 እንደተሻሻለው መሠረት ለተመራጭነት በእጩነት ለመመዝገብ የፈለገ ማንኛውም ሰው
• ኢትዮጵያዊ ዜጋ መሆን
• በድምጽ መስጫው ዕለት እድሜው 21 ዓመት ወይም ከዚያ በላይ መሆን
• ከምርጫው ዕለት አስቀድሞ በምርጫ ክልሉ ውስጥ በመደበኛነት አንድ ዓመት ከኖረ ወይም የትውልድ ቦታው በእጩነት ሊቀርብበት በፈለገበት የምርጫ ክልል ውስጥ መሆን
• በሕግ ወይም በፍርድ ቤት ውሳኔ የመመረጥ ወይም የመመረጥ መብቱ ያልተገፈፈ መሆን
• በአዕምሮ ህመም ምክንያት ለመወሰን ብቃት የሌለው መሆኑ ስልጣን ባለው አካል ወይም በበቂ ማስረጃ ያልተረጋገጠበት መሆን ይጠበቅበታል፡፡
ከላይ ከተዘረዘሩ መመዘኛዎች በተጨማሪ በግል የቀረበ እጩ ማለትም የግል ተመራጭ በአካባቢው መስተዳድር የተረጋገጠ እድሜያቸው 18 ዓመትና ከዚያ በላይ ከሆናቸው እና የመምረጥ መብታቸው በሕግ፣ በፍርድ ቤት ውሳኔ ወይም በአዕምሮ ህመም ምክንያት ያልተገደበ የምርጫ ክልሉ ነዋሪዎች ውስጥ ከአምስት ሺ የማያንስ የድጋፍ ፊርማ ማቅረብ እንዳለበት በአዋጁ ላይ በአስገዳጅነት ተደንግጓል።፡፡ በልዩ ሁኔታ የግል እጩ ተወዳዳሪው የአካል ጉዳተኛ ከሆነ ማቅረብ ያለበት የድጋፍ ፊርማ ብዛት ከሶስት ሺ የማያንስ መሆን እንዳለበት ተመልክቷል።
የምርጫ መርሆዎች
ምርጫ ሊያሟላቸው የሚገቡ መርሆዎች በአዋጁ አንቀጽ 5 ተመልክተዋል፡፡ ይኸውም
• ማንኛውም ምርጫ ሁሉን አቀፍ፣ ቀጥተኛ፣ በምስጢር ድምፅ አሰጣጥ መራጩ ፈቃዱን በነፃነት የሚገልጽበት እና ያለ ምንም ልዩነት በሚደረግ ህዝባዊ ተሳትፎ ላይ የተመሰረተ መሆን
• የመምረጥ ወይም የመመረጥ መብቱ በህግ ወይም በፍርድ ቤት ውሳኔ ያልተገደበ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ መምረጥ ወይም መመረጥ መብቱ የተጠበቀ መሆን እና ለመምረጥም ሆነ ለመመረጥ ያለመገደድ
• የእያንዳንዱ መራጭ ድምፅ እኩል መሆን
• እያንዳንዱ መራጭ ድምጽ መስጠት የሚችለው በአካል በመገኘት መሆን ናቸው፡፡

በምግብ ዉስጥ መርዝ በመጨመር የግድያ ወንጀል የፈፀመችዉ ወጣት በእስራት ተቀጣች***

Published on: February 11, 2026 at 4:55 PM
ተከሳሽ ሱመያ ሙሳ አብራሂም የተባለችዉ የ15 አመት ወጣት በሀረሪ ክልል ድዬ ጠያራ ወረዳ ሚያይ ቀ/ገ/ማህበር ገንደ አመድ በሚባል ስፍራ ግንቦት 3 ቀን 2017 ዓ.ም በግምት ከቀኑ 7:00 ሰአት ተከሳሽ የሆነዉ ይሁን የሚመጣዉን ዉጤት ለመቀበል አስቀድማ በማሰብ ለተበዳዮቹ ባዘጋጀችዉ የሳህን ምግብ ዉስጥ መርዝ በመጨመር ታጁ አሊ የተባለዉ ምግቡን ሲመገብ በመመረዙ ሂወቱ ሲያልፍ ሌላኛዉ የግል ተበዳይ ፌሮምሳ ሸሪፍ ምግቡን ተመግቦ ቢመረዝም ህክምና ተደርጎለት የተረፈ በመሆኑ ተከሳሽ በፈፀመችዉ ሰዉ የመግደል ወንጀል በሁለት ተደራራቢ ክስ ተከሳለች።
ተከሳሽ በ1996 ዓ.ም የወጣዉን የኢ.ፌ.ድ.ሪ የወንጀል ህግ አንቀፅ 58(1)(ለ) እና 540 እና በተመሳሳይ በ1996 ዓ.ም የወጣዉን የኢ.ፌ.ድ.ሪ የወንጀል ህግ አንቀፅ 27(1)58(1)(ለ)እና 540 ላይ የተደነገገዉን በመተላለፍ ተከሳለች::
ጉዳዩን የያዘዉ የሀረሪ ጠቅላይ አቃቢ ህግ ልዩ ልዩ ወንጀሎች ዳሬክቶሬት አቃቢ ህግ የተፈፀመዉን ወንጀል በሰዉናበሰነድ ማስረጃ ካጠናከረ በኃላ ለክልሉ ከፍተኛ ፍ/ ቤት ጉዳዩን ያስረዳ በመሆኑ ፍርድ ቤቱ ዛሬ 21/5/2018ዓ.ም በዋለዉ ችሎት ተከሳሽ በ17 አመት እስራት እንድትቀጣ ወስኗል።

የፕላስቲክ ከረጢቶች /ፌስታል ምርቶችን/ መጠቀም የሚያስከትለው ተጠያቂነት

Published on: February 11, 2026 at 4:53 PM
መግቢያ
ኢትዮጵያ ከሕገ መንግስቱ ጀምሮ የአካባቢ እንክብካቤን የተመለከቱ ሕጎች ያሏት ሲሆን የሁሉም ሕግ የበላይ ከሆነው ሕገ መንግስታችን ብንነሳ በአንቀጽ 44/1/ ስር ሁሉም ሰዎች ንጹህና ጤናማ በሆነ አካባቢ የመኖር መብት እንዳላቸው ይደነግጋል። በዚሁ ሕገ መንግስት አንቀጽ 92 ስር መንግስት ሁሉም ኢትዮጵያዊ ንጹህና ጤናማ በሆነ አካባቢ እንዲኖረው ጥረት የማድረግ ኃላፊነት እንዳለበት ተደንግጓል። በዚህ መነሻነት የወንጀል ሕጉ እና ሌሎች አዋጆች ለምሳሌ የደረቅ ቆሻሻ አያያዝ አዋጅ ቁጥር 513/1999 ተግባራዊ ሲደረግ የቆየ ሲሆን ከጉዳቱ መጠን እና በኢትዮጵያ ካለው የስርጭት አድማስ አንጻር በተለይ የፕላስቲክ ምርትን አስመልክቶ የሕግ ማእቀፍ መዘርጋት አስፈላጊ ሆኗል። ስለሆነም የፕላስቲክ ምርቶችን መጠቀም የሚከለክል አለፍ ሲልም የወንጀል ቅጣትን የሚደነግግ አዋጅ ቁጥር 1386/2017 ወጥቶ በስራ ላይ ውሏል።
የፕላስቲክ ምርት/ፌስታል/ ምንነት
በአዋጅ ቁጥር 1383/2017 አንቀጽ 2/9/ ስር እንደተደነገገው ፕላስቲክ ማለት በዋናነት ከፔትሮኬሚካል የተሰራ፣ ለስላሳና የማይበሰብስ የፖሊመር ይዘት ያለው ምርት እንደሆነ ትርጉም ተሰጥቶታል። ይህም በተለምዶ ፌስታል ተብሎ የሚጠራውን ምርት የሚያመለክት ነው። በዚሁ አዋጅ አንቀጽ 2/10/ ስር እንደሰፈረው የፕላስቲክ ከረጢት ማለት አነስተኛ ጥግግት ያለው፣ በቀላሉ በስብሶ ከአፈር ጋር የማይዋሃድ እና ሌሎች ምርቶችን ለመያዝ የሚያገለግል ፕላስቲክ እንደሆነ ተመላክቷል። ይኸውም የፌስታል ከረጢትን የሚያመለክት ነው።
ከዚህ ጋር ተያይዞ የሚነሳው የስስ ፌስታል ጉዳይ ሲሆን በአዋጁ አንቀጽ 2/11/ ስር አንድ ጊዜ ጥቅም ላይ የሚውል ፕላስቲክ የሚል ስያሜ የተሰጠው ሲሆን ይኸውም መልሶ ጥቅም ላይ የማይውል ወይም መልሶ ኡደት የማይደረግ እና አንድ ጊዜ ብቻ ጥቅም ላይ ውሎ ቀጥታ የሚወገድ የፕላስቲክ ምርት እንደሆነ በዚሁ ድንጋጌ ተገልጿል።
በፕላስቲክ ምርት/ፌስታል/ ላይ የተደረገው ክልከላ
ለአንድ ጊዜ ጥቅም ላይ የሚውል ፕላስቲክ/ በተለምዶ ስስ ፌስታልን/
• መጠቀም ወይም ለመጠቀም ይዞ መገኘት፣
• ማምረት፣ ወደ አገር ውስጥ ማስገባት፣ ለገበያ ማቅረብ፣ መሸጥ፣ ለንግድ ዓላማ ማከማቸት ወይም ይዞ መገኘት ክልክል መሆኑን እና አስተዳደራዊ ተጠያቂነትን እንደሚያስከትል በአዋጁ አንቀጽ 24/9/ ስር ተደንግጓል። ሆኖም ግን የፌዴራል አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ለአንድ ጊዜ ብቻ ጥቅም ላይ የሚውሉ ፕላስቲኮች እንዲመረቱ ወይም ጥቅም ላይ እንዲውሉ በልዩ ሁኔታ በመመሪያ ሊፈቅድ እንደሚችል በአዋጁ አንቀጽ 14 ስር ተደንግጓል።
የወንጀል ተጠያቂነት
በአዋጁ አንቀጽ 25 ስር ክልከላዎችን መተላለፍ የወንጀል ተጠያቂነትን እንደሚያስከትል ተደንግጓል። ይኸውም፡-
• ማንኛውም ሰው የፕላስቲክ ከረጢት/የፌስታል ከረጢት/ ከተጠቀመ ወይም ለመጠቀም ይዞ ከተገኘ ከ2,000/ሁለት ሺህ ብር/ በማያንስና ከ5,000/አምስት ሺህ ብር/ በማይበልጥ የገንዘብ መቀጮ ይቀጣል።
• ማንኛውም ሰው የፕላስቲክ ከረጢት/የፌስታል ከረጢት/ ካመረተ ወይም ወደ አገር ውስጥ ካስገባ፣ ለገበያ ካቀረበ ወይም ከሸጠ፣ ለንግድ ዓላማ ካከማቸ ወይም ይዞ ከተገኘ ከ50,000/ሀምሳ ሺህ ብር/ በማያንስና ከ200,000/ሁለት መቶ ሺህ ብር/ በማይበልጥ የገንዘብ መቀጮ እና ከ5/አምስት አመት/ በማይበልጥ ጽኑ እስራት ይቀጣል፡፡ ይኸውም የፕላስቲክ ከረጢት/ፌስታል/ ከግለሰባዊ አገልግሎት ውጪ ለንግድ ዓላማ ጥቅም ላይ ሲውል ከገንዘብ ቅጣት በተደራቢነት በእስራት እንደሚያስቀጣ መረዳት ይቻላል።
• ከላይ የተመለከቱትን የወንጀል ድርጊቶች የፈጸመው ሕጋዊ ሰውነት ያለው ድርጅት ከሆነ የገንዘብ ቅጣቱ ከላይ የተገለጸውን 3/ሶስት እጥፍ/ ይሆናል።

ተቋማዊ የመረጃ ቋት ለተጠናከረ የሥራ ግልፀኝነት

Published on: October 10, 2025 at 5:05 PM
ተቋማዊ የመረጃ ቋት ለተጠናከረ የሥራ ግልፀኝነት
****
የሀረሪ ጠቅላይ አቃቤ ህግ ቢሮ የተቋሙን የአገልግሎት ተጠቃሚዎችና መረጃ ፈላጊዎችን ፍላጎት ለማርካትተቋማዊ የሥራ ግልፀኝነትን ከማጠናከር ፤ የተጠቃሚውን አካል የሕግ ዕውቀትን ከማሻሻል እና ግንዛቤ እንዲኖራቸው ለማስቻል ድረ-ገፅ ተከፍቷል፡፡
ይህ ድረ-ገፅ በተለያዩ ጊዜያት የወጡ እንዲሁም ወቅታዊ የሆኑ አዋጆችንና መመሪያዎችን ያሉበትን ደረጃ ማለትም በትግበራ ላይ ያሉ እንደሆነ፣ የተሻሩ እና በከፊል የተሰሩ እንደሆነ በሚያሳይ መልኩ መረጃዎችን ለህብረተሰቡ ተደራሽ ያደርጋል፤ የአስተዳደር ሥነ-ሥርዓት አዋጁን ተከትሎ በተቋማት የሚወጡና የተመዘገቡ መመሪያዎችን ለህዝብ ያደርሳል እንዲሁም የማህበረሰብ ፍትሕ አገልግሎት ሥራዎችን ይዳስሳል፡፡
በዋናነት በድረ-ገፁ የተለያዩ አዋጆች፤ መመሪያዎችንና ዓለማቀፍ ስምምነቶችን፤ ወቅታዊ ዜናዎችና ሪፖርቶች፤ የዜና መግለጫዎችን፤ ግንዛቤን የሚያስጨብጡ ፅሁፎችን፤ የተቋሙን ድርጅታዊ መዋቅር መሰል ጉዳዩችን ለመረጃ ፈላላጊዎች እና ለተቋሙ አገልግሎት ተጠቃሚዎች በቀላሉ ማግኘት በሚያስችል እና ግልፅ በሆነ መልኩ ይዞ ቀርቧል፡፡
ለእናንተም የተከበራችሁ የማህበራዊ ሚዲያ ትስስር ገጾቻችን ተከታዩች በአዲስ መልኩ የለማውን የተቋማችንን ድረ-ገፅ ከዚህ በታች የተቀመጠውን ሊንክ በመጫን እንድትጠቀሙ በአክብሮት ተጋብዛችኋል፡፡
የሀረሪ ጠቅላይ አቃቤ የማህበራዊ ሚዲያ ትስስር ገፆችን ይቀላቀሉ
Website፡-www.hararattorney.gov.et
Facebook ፡-Harari Region Attorney General
ተቋማዊ የመረጃ ቋት ለተጠናከረ የሥራ ግልፀኝነት

todays

Published on: September 30, 2025 at 2:01 PM
news
todays

Attorney

Published on: September 28, 2025 at 7:38 PM
As you say
Attorney